Wednesday, 22 February 2017

ሰላም፡ አንድነት፡ ተስፋ (ሰማያዊ)


ሰማያዊን አስመልክቶ  ፓርቲው እንደፈረሰ እንዲሁም አዲሶቹ ተመራጮች ላይ በተለይም አዲሱን ሊቀመንበር አቶ የሺዋስ አሰፋ ላይ አሮጌው ፍረጃ እየወረደ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በተቃውሞ ጎራው ጉዳይ ላይ ደጋግሜ እንዳልኩት ፈረጃ ስልጡኑን ቁጭ ብሎ የመነጋገር እድልን የሚዘጋ አሮጌ መንገድ ነው፡፡ ይህም የተቃውሞ ጎራውን አንካሳ ሲያረግ የኖረ ነው፡፡ ላንዳንዶች ፓርቲ የግለሰቦች ንብረት ይመስላቸዋል፡፡ ለዚህ ነው ግለሰቦቹ ሲሄዱ የሚፈርስ እነሱ እስካሉ የሚቆም የሚመስላቸው፡፡ ለምሳሌ ኢ/ር ይልቃል የነበረውን ችግር ለመፍታት እድሉ በእጁ ነበር፡፡ ሌላው ሁሉ ቀርቶ በጠቅላላ ጉባኤው ላይ ተሳትፎ መሟገት ይችል ነበር፡፡ በእጁ የነበሩትን መድረኮች ከመጠቀም ይልቅ ዳር ዳር ሲል ቆይቶ በመጨረሻ አማራጭ ያደረገው አሮጌውን መንገድ ነው፡፡ በግለሰቡ ፍቅር የወደቁ ተከታዮቹም ከዛ የተሻለ ነገር ማድረግ አልቻሉም፡፡


በጣም የሚገርመው  በማንኛውም ተቋማት ውስጥ በመሪነት ላይ ያሉ ሰዎች ጥሩ ነገር ሲሰራ መመስገናቸው ያለ በተቃራኒው ሲሆን ደግሞ ተጠያቂ የሚሆኑበት ሁኔታ ያለ ቢሆንም በኢትዮጵያ የተቃውሞ ጎራ ውስጥ ግን ለሚሰሩ ስህተቶች ሌሎችን ‹‹ወያኔ›› ማለት እራስን ከስህተት ነፃ የሚያደርግ ነው፡፡ ይህን ሳይመረምሩ አሁንም ላለፉት ሁለት አስርታት በተሄደበት መንገድ ለመሄድ መጣደፍ ሌሎች ሁለት አስርታትን ቁጭ ብሎ ከመቁጠር የዘለለ ነገር አያመጣም፡፡ ለግለሰቦች ከማልቀስ በዘለለ ፓርቲዎች የለውጥ እንቅስቃሴውን መሸከም የሚያስችል አቅም እንዲፈጥሩ ከማገዝ ይልቅ የሥነ-ሥርዓት ኮሚቴው ላይ እንደሆነው የበላይ አመራሮችን የመጠየቅ አቅም መፍጠሩ ከማስመስገን ይልቅ የአሮጌው ፖለቲካ ሰለባ ነው ያደረገው፡፡ በዚህ ሁኔታ እንዴት ተቋማዊ ቅርፅ ያለው የለውጥ ሀይል እንደሚፈጠር ግራ ያጋባል፡፡



ሌላው አንድነት ላይ የሆነውን በማንሳት የሰማያዊም ተመሳሳይ እንደሆነ ለመግለፅ የሚሞከረው ከላይ ለማንሳት እንደሞከርኩት እራስን ከስህተት ነፃ ለማድረግ እንዲሁም ካፈርኩ አይመልሰኝ ነው፡፡ ሌላው ሁሉ ቀርቶ አንድነት ውስጥ ከተፈጠረው ችግር ጀምሮ አባላት ከፅህፈት ቤታቸው በፖሊስ ሃይል እንዲወጡ ተደርጎ  ለአቶ ትዕግስቱ አይነት መካሪ አልባ ሰው ፓርቲው እስኪሰጥ አብሮት የነበረው ከፍ ካለው የፓርቲው መዋቅር  አንድ ግለሰብ ብቻ ነው፤ አባል የነበሩት በጣት የሚቆጠሩ ነበሩ ሌሎች ከየት እንደመጡ እንኳን አይታወቅም፡፡ በሰማያዊ ውስጥ በብቸኝነት በሚመስል መልኩ አቶ የሺዋስ ላይ ፍረጃ የሚያካሂዱት እንደ አቶ ትዕግስቱ ከምርጫ ቦርድ ሰማያዊን በችሮታ ያገኘ ለማስመሰል ነው፡፡ ለዚህ ነው በጠቅላላ ጉባኤ ስለተሳተፉ ግለሰቦች፣ስለብሔራዊ ምክር ቤት አባላት፣እንዲሁም አሁን ስላሉት ስራ አስፈፃሚ አባላት ትንፍሽ ሲሉ የማይሰማው፡፡ ይህ የአሮጌው ፖለቲካ ሌላው ምሳሌ ነው፡፡



ከላይ እንዳልኩት ይህ አሮጌ ፖለቲካ ውዥንብር በመፍጠሩ ሰማያዊን አንካሳ ሊያደረግ እንደሚሞክር ግልፅ ነው፡፡ አሁን ያለው አመራር ለዚህ ጆሮ ሳይሰጥ ቆፍጠን ብሎ ጥሩ የሚባሉትን በማጎልበት ያለፉትን ህፀፆች በመመርመር ለምሳሌ በውስጠ ዲሞክራሲ እና በተቋማዊነት ላይ ጠንክሮ መስራት ይጠበቅበታል፡፡ ባጠቃላይ  የተቃውሞ ፖለቲካውን የአሮጌው ፖለቲካ መፈንጫ ከመሆን ለመታደግ መስራት የሁሉም የለውጥ ሀይል ድርሻ ነው፡፡

የትም የማያደርሰው አሮጌው ፖለቲካ…


ሰማያዊን አስመልክቶ ከዚህ ቀደም ያሉበትን ክፍተቶች አርሞ ወደፊት እንዲጓዝ በማሰብ የተወሰነ ነገር ብያለሁ፡፡ ይህንን ሳደርግ እንዲሁ በቀቢፀ ተስፈኛነት ሳይሆን ይህንን ማድርግ የሚያስችል አቅም በሰማያዊ ውስጥ አለ ከሚል ነው፡፡ ነገር ግን  እንዳየነው ችግሮቹ እንዳይፈቱ ጋሬጣ ከሆኑ አጥሮች ተሻግሮ መስራት አልተቻለም፡፡ ፖለቲካውን የከበቡት አካላትም ችግሮቹን ለመመልከትና የመፍትሄው አካል ከመሆን ይልቅ ትላንት በተሄደበት መንገድ ለመሄድ ያንኑ የመረጡ ይመስላል፡፡ ፍላጎታችን የተቃውሞ ጎራው በተለያየ ፓርቲ ስም የመቃወም እና የመቃወም ተግባሩን ብቻ እንዲቀጥል ከሆነ ይህ ተግባር በቂ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ መንገድ ግን የተቃውሞ ጎራውን መንግስት ለመሆን አያስችለውም፡፡ የፓርቲ ፖለቲካ ትግል ስልጣን ለመያዝ ነው፡፡ ይህ ገዢዎች እና አንዳንዶች ለራሳቸው ሲሉ ጠበብ አድርገው  እንደሚተረጉሙት የስልጣን ጥማት ሳይሆን ያሉትን ፕሮግራሞችና ፖሊሲዎች ለማስፈፀም ስልጣን መሳሪያ ስለሆነ ነው፡፡ነገር ግን ወደ ፓርቲ የሚመጡት በሙሉ ከላይ ያለውን ታሳቢ አድርገው ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ 


ፍላጎታችን የተቃውሞ ጎራ መንግስት የመሆን አቅም እንዲፈጥር ከሆነ ትላንት የሄድንባቸውን ብቻም ሳይሆን ዛሬም እየሄድንባቸው ያሉትን መመልከት መቻል አለብን፡፡ ከዚህ ቀደም ፅሁፌ ሰማያዊ የሚያደርገው ጠቅላላ ጉባኤ ፈተናቹን አልፎ ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚሸጋገርበት መሆን እንዳለበት አሳስቤያለሁ፡፡ ነገር ግን ይህን በውሃ ቀጠነ አንዳይሳካ ሲጥሩ ተመልክተናል፡፡ ቅንነቱ ብቻም ሳይሆን ለተቋማዊነት የመገዛት አቅሙ ካለ መተባበር እንጂ ፖለቲካውን አድሮ ቃሪያ ያደረገውን አሮጌ ፖለቲካ ተደግፎ ለማምለጥ ዝምታን መምረጥ ከዛም ሁኔታው ወደፊት ገፍቶ መሄዱ ሲታወቅ ‹‹ጠቅላላ ጉባኤው እየተካሄደ ያለው ምንጩ ባልታወቀ ገንዘብ ነው›› ማለት ከዛም አልፎ አዲስ መሪ ሲሾም ‹‹የፓርቲው ደንብ ተጥሷል›› ብሎ ማልቀስ መልስ ሳይሆን በግልፅ ቋንቋ ካፈርኩ አይመልሰኝ ነው፡፡


ለምሳሌ የኢ/ር ይልቃል ካቢኔ በቁጥር እንኳ ያልተሟላ መሆኑ ብቻም ሳይሆን እንደ ባህር ዳሩ ሰልፍ አይነት ውሳኔዎችን በደፈናው ወስኖ ከተቁዋማዊነት ውጪ በሆነ መንገድ ሰልፉ ሊካሄድ ከአስራ ሁለት ሰአታት በታች በቀሩበት ሁኔታ ያስተባበለበት መንገድ የአመራሩን ድክመት በግላጭ ያሳየ ነው፡፡ ከተጠያቂነት አንፃር የተካሄደው ቸልተኝነት ለምሳሌ ያክል የሥነ-ሥርዓት ኮሚቴውን ውሳኔ የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን አግዶ ያቆየበት መንገድ፤ እንደገባኝ በብዙ ተፅእኖም ውስጥ ሆኖ  ነገሩን በቅንነት ለማየት ከመሞከር ይመስለኛል ቢሆንም ፓርቲውን ወደፊት ሊያራምድ አልቻለም፡፡ ይባሱኑ  ብዙ የፓርቲ አባላቶችን  አስከፍቶ ከፓርቲው እንዲሸሹ ምክንያት ሆኗል፡፡



 ኢ/ር ይልቃል ከአዲስ አድማስ ጋር ያደረገውን ቃለ ምልልስ ሳነብ  በስም እየጠቀሰ እነዚህን የመሰሉ የፓርቲው አባሎች የመባረር ውሳኔ ተላልፎባቸዋል ይልና ‹‹ታዲያ እነዚህን ሁሉ አመራሮች የሚያባርር አካል፣አላማው ምንድን ነው? ይሄ ሆን ብሎ ፓርቲውን ለማፍረስ የሚደረግ እንቅስቃሴ ነው፡፡›› በኢ/ር ይልቃል አገላለፅ የጠቀሷቸው ግለሰቦች ድርጅት/ፓርቲ ሆነዋል ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው ቀድሞውኑ ፓርቲው ያስቀመጠውን መንገድ መከተል ያልፈለጉት፡፡ ይህ ደግሞ ለተቋማዊነት አለመገዛትም ነው፡፡ የፓርቲው የስነ-ስርዓት ኮሚቴ የበላይ አመራሮችን የመጠየቅ አቅም መፍጠሩ ከማስመስገን ይልቅ የአሮጌው ፖለቲካ ሰለባ ነው የሆነው፡፡ ኢ/ር ይልቃልም በዘወርዋራ ያለው አዲስ ሳይሆን አሮጌው የፍረጃ ፖለቲካ ነው፡፡ ይህን አሮጌ የፍረጃ ፖለቲካ እንዲቀጥል የሚያግዙ ሰዎችም የሚያቀርቡት የሞተ አመክንዮም መሬት ላይ ያለውን እውነታ የሚያንፀባርቅ ሳይሆን ይህንኑ አሮጌ ፖለቲካ የተደገፈ ነው፡፡ የሚሰሙ ከሆነ የትኛውም የፓርቲ አባል ጠያቂ መሆኑ የሚደገፍ ቢሆንም ጠያቂ ስለሆነ ተብሎ የማይነካና የማይጠየቅበት ምክንያት የለም፡፡



ፓርቲው በሰኔ ወር 2007 ዓ.ም ሁለተኛውን ጠቅላላ ጉባኤ ካደረገ በኋላ በፖለቲካው በኩል ምንም የጎላ እንቅስቃሴ አላደረገም፡፡ በእነዚህ ጊዜያት ችግሮች መኖራቸው የሚታወቅ እንደመሆኑ መጠን በአመራሩ ይህ እንዲፈታ አባላት ተጠርተው እንኳን ውይይት አልተደረገም፡፡ ይህ ሁሉ ባለበት ሁኔታ ፓርቲው ለጠቅላላ ጉባኤ በሚዘጋጅበት ወቅት ለዚህ አጋዥ ሆኖ ከመሰለፍ ይልቅ ሁኔታውን  ችላ በማለት ከዚህ ፅሁፍ ጋር ተያይዞ የቀረበው ምስል እንደሚያሳየው  መስከረም 24 2009 ዓ.ም ሃምሳ የማይሞሉ የፓርቲው አባላት ባሉት በወቅታዊ ጉዳዮችና በፓርቲው የወደፊት የስራ እንቅስቃሴ ዙሪያ ከአባላት ጋር ውይይት ተካሄደ፤ የሚል ዜና ተሰራ፡፡ በፓርቲው  ውስጥ ያለው ችግር እንዲስተካከል ሳይጥሩ  በምስሉ እንደሚታየው ከተሰብሳቢዎቹ መጀመሪያ ላይ ያለው አቶ ስለሺ ፈይሳ እና መሰሎቹ  በአዲሱ አመራር  በቅርቡ በፓርቲው ፅ/ቤት ሊካሄድ በታቀደው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በመገኘት ህጋዊ ሊቀመንበሩ ኢ/ር ይልቃል ነው፤እናንተ ህገ-ወጦች ናችሁ በማለት ወደ ግብግብ ያመሩበት ሁኔታ ከግለሰብ ፍቅር ውጪ ሌላ ነው ብዬ ማሰብ ይቸግረኛል፡፡ ይህ ደግሞ የትም አያደርስም፡፡


አንዳንዶች በግርድፉ የሰማያዊን ሁኔታ ከአንድነት ጋር አንድ ሊያደርጉት ይሞክራሉ፡፡ አንድነት ውስጥ የሆነው ከዚህ በጣም የተለየ ነው፡፡ ይህን መረዳት የሚፈልግ መለስ ብሎ ማየት ይኖርበታል፡፡ እዚህ ጋር ግን መርሳት የሌለብን ግለሰቦች በተለይም በአመራር ደረጃ ያሉ ሰዎች በሚፈፅሙት ስህተት የሚፈጠሩትን ችግሮች እስከመቼ በፍረጃ እና በገዢዎቹ እያሳበብንና ስህተቱን የሰሩትን ነፃ እያደረግን እንቀጥላለን? ይህ ለተቃውሞ ጎራው የስህተት መደበቂያ አይሆንም ወይ? እዚህ አገር በተለይ ፓርቲዎች ከመቋቋም ጀምሮ በገዚዎች ተፅእኖ እንደሚደርስባቸው እሙን ነው፡፡ ይህ ከሆነ ለዚህ መሻገሪያን መንገድ ማዘጋጀት የእነሱ ተግባር አይደለም ወይ? ለዚህም ሃላፊነቱን መውሰድ የለባቸውም ወይ? ይህን ሳንመልስና አለባብሰን አሮጌውን ፖለቲካ መከተል የትም የማያደርስ ብቻም ሳይሆን አንድ እግር ወደፊት አንድ እግር ወደኋላ አይነት ነው፡፡


አሁን የፓርቲው ሊቀመንበር ሆኖ የተመረጠው አቶ የሺዋስ ከኢ/ር ይልቃል ጋር ከአንድነት ‹‹መርህ ይከበር›› ብሎ የወጣ ብቻም ሳይሆን የብሔራዊ ምክር ቤቱ ሰብሳቢ ሆኖ ሲሰራ የቆየ ነው፡፡ በዚህም ጊዜ ለእስር ተዳርጎ ሁለት አመታት ለሚጠጋ ጊዜ በእስር የቆየ ነው፡፡ አሁን በአፍራሽነት የሚፈረጀው እሱ ብቻ ሳይሆን ሰማያዊ ተቋማዊ ቁመና ያለው የለውጥ ሀይል ሆኖ እንዲወጣ ደፋ ቀና ያሉትም ጭምር ናቸው፡፡ የተቃውሞ ጎራው ተዋናዮች ከትላንት ስህተት ከመማር ይልቅ ዛሬም በአሮጌው መንገድ ለመትመም የሚጣደፉ ነው የሚመስለው፤ አሁን አሁን እንደምናየው የፓርቲ አባላት ወደ ፓርቲ ሲመጡ ስርዐቱን ከመጥላት በዘለለ፤ ርዕዮተ አለም፣ ተቋማዊነት እና በውስጠ ፓርቲ ዲሞክራሲ  ከመሳብ ይልቅ በግለሰቦች ፍቅር ወድቀው ነው አባል የሚሆኑ የሚመስለው፤ ከዚህ አኳያ እነዚህ ሰዎች ሌላው ሁሉ ቀርቶ በምክንያት ክርክር ያደርጋሉ ብሎ ማሰብ ያስቸግራል፡፡ ከዚህ አኳያ የተቃውሞውን ጎራ ከጅምሩ የምክንያት ሜዳ ከማድረግ ይልቅ የአሮጌው ፖለቲካ መፈንጫ ሆኗል፡፡ ይህ ሳይዘምን እና ሳይስተካከል መንግስት መሆን አቅም ይፈጠራል ማለት ዘበት ነው፡፡

Tuesday, 27 September 2016

የሰማያዊ ፓርቲ ፈተናዎች እና ተስፋዎች…


ሰማያዊ ፓርቲ በሰኔ ወር 2007 . ሁለተኛውን ጠቅላለ ጉባኤ ካደረገ በኋላ በፖለቲካው በኩል የጎላ እንቅስቃሴ ከማድርግ ይልቅ በውስጥ ችግሮች ተወጥሮ ሁኔታው አሁን ያለበት ደርሷል፡፡ ከዚህ በፊት በተለይ በፓርቲ ውስጥ ግልፅነትና ተጠያቂነትን አስመልክቶ እንዲሁም የተቃውሞ ጎራው አሁን ካለበት ተጠናክሮ እንዲወጣ ያስችለዋል ያልኩትን ሃሳብ እዚህ መድገም ስለማያስፈልግ ሊንኩን ኮሜንት መስጫው ላይ አስቀምጬ አልፋለሁ፡፡

-በቅርቡ ብሔራዊ ምክር ቤቱ ተሰብስቦ በፓርቲ መተዳደሪ ድንብ አንቀፅ 10/6 መሰረት የስራ አስፋፃሚውን የመተማመኛ ድምፅ ነፍጎታል፡፡ በዚህም መሰረት የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ጠቅላላ ጉባኤ ለማካሄድ ሃላፊነቱን ተረክቦ ለዛሬ 14/01/2009 . ጠቅላላ ጉባኤ እንደሚካሄድ አስታውቆ ነበር፡፡ ሆኖም ከምርጫ ቦርድ በተላከ ደብዳቤ ማለትም ምርጫ ቦርድ ከጉባኤው በፊት ማጣራት ያለብኝ ጉዳይ ስላለ ጉባኤውን እንዲተላለፍ ሲል ጠይቋል፡፡ በዋነኝነት በዚህ ምክንያት ጉባኤው ሳይካሄድ ቀርቷል፡፡

የሆነው ሆኖ በፓርቲ ወስጥ ግልፅነትና ተጠያቂነት መኖሩ ሊደገፍና ሊበረታታ የሚገባው ተግባር ነው፡፡ የዛሬውን ብቻም ሳይሆን ነገ እንዲሆን የምንፈለገውን ለማየት የምንሻ ከሆነ ግልፅነትና ተጠያቂነት ለተቃውሞ ጎራው የህልውናም ጉዳይ ነው! ስለሆነም ሰማያዊ ፓርቲ እንደ አንድ አማርጭ ሃይል ሆኖ እንዲወጣ የምንፈልግ ከሆነ ለግለሰቦች ከማልቀስ በዘለለ ፖለቲካው እንዲዘምን ተነሳሽነት ማሳየት አለብን፡፡ አሁን እንደምናየው አሮጌውን የፍረጃ ፖለቲካ ማካሄድ ትንሽም ቢሆን የተካበውን ከማፍረስ ውጪ የሚፈይደው ነገር የለም፡፡ ግለሰቦቹንም አይጠቅምም፣ ፓርቲውንና ትግሉንም አይጠቅምም፡፡

የተቃውሞ ጎራው የቅዱሳን ስብስብ አይደልም፡፡ አለመግባባቶች ሊኖሩ ይችላሉ፤ይህ ሲፈጠር የትኛውንም እርቀት ተሂዶ በፓርቲ አጥር ውስጥ ከመፍታት ይልቅ የተለመደውን እና ትላንት ለብዙ ግዜ ተሂዶበት ለውጥ ያላመጣውን መንገድ መምረጥ ምን የሚሉት ነው? እዚህ ላይ አንዳንዶቹ በውጭ ተቀምጠው በበርካታ ፈተናዎች ውስጥ የሚያልፉትን በሰርጎገብነት ሲፈርጁ መመልከት አዲስ አይደልም፡፡ ቆይ እስኪ በፓርቲ ውስጥ ያሉ የትኞቹም ክፍሎች ደካሞች ቢሆኑ ለፓርቲው ምን ይጠቅማሉ? ጥርስ የሌለው ብሄራዊ ምክር ቤት፣ጥርስ የሌለው የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ምን ይስራል? እነዚህ ክፍሎች የበላይ አመራሮችን የመጠየቅ አቅም በመፍጠራቸው ሊበረታቱ ሲገባ ዛሬም አንደትላንቱ በሰርጎገብነት ፈርጀን እንዴት ተቋማዊ ቁመና ያለው የለውጥ ሃይል መፍጠር እንችላለን?

ፖለቲካ የህዝብ እስከሆነ ድርስ በድብቅና በይሉኝታ የሚሰራ መሆን የለበትም፡፡ በጓደኝነት በሌላም በሌላም ምክንያት ጠበቃ ሆነው ሌላው ላይ ፍረጃ ሲያካሂዱ ይታያል፡፡ ይህ የተካበውን ከማፍረስ ውጪ አንዳችም የሚፈይደው ነገር የለም፡፡ እንደውም የፍረጃ ትልቁ ችግር ወርቃማውንና ስልጡኑን በመከባበርና በእኩልነት ቁጭ ብሎ የመነጋገር እድልን መዝጋቱ ነው፡፡ ዛሬ እከሌ ሰርጎገብ ነው ብሎ ነገ በምን አይነት መንፈስ ነው ከእርሱ ጋር ቁጭ ብሎ መነጋገር የሚቻለው? ለማንኛውም ጠያቂ የለውጥ ሃይሎችን ጠያቂ በመሆናቸው ብቻ ተጠያቂ የማይሆኑበትን ሁኔታ ሊፈጥር አይገባም፡፡ መጠየቃቸው በምንም መንገድ እንደነውር መታየት የለበትም፡፡ ሊያስጨንቀን የሚገባው የግለሰቦቹ መጠየቅ ሳይሆን ከፍረጃና ከስሜት በመሻገር ነገ መፍጠር ለምንፈልገው ስርዐት መሰረቱን እያስቀመጥን ነው ወይስ አይደለም? የሚለው ነው፡፡

ፓርቲው ከፊቱ አሮጌው የፍረጃ ፖለቲካ፣የግለሰቦች አምልኮ እንዲሁም ከተጠያቂነት ጋር ተያይዞ ያሉት ነገሮች ጋሬጣ ሆነውበታል፡፡ ካለፈው ስህተት ጭምር በመማር ይህን መሻገር ካልተቻለ አድሮ ቃሪያ ከመሆን አይዘልም፡፡ ቁም ነገሩ ዛሬ ተሰብስበን ነገ መበታተናችን አይደልም፡፡ በመንገዳችን አስር ጊዜ ልንወድቅና ልንነሳ እንችላለን ነገር ግን ካለፈው ምን ይዘን መጣን? ከውድቀታችንስ ምን ተማርን? ነገስ የትኛውን መንገድ እንመርጣለን? ያሰብንበት እንድንደርስስ የትኛው መንገድ ይጠቅመናል? የሚለው መመለስ ያለበት ነው፡፡

በእርግጠኝነት የፓርቲው አባላት ከላይ ያለውን ከመለሱ ከፊታቸው ያለውን ፈተና የማለፍ ተስፋ አለ፡፡ እኔ በዚህ በኩል ተስፋ አልቆርጥም፤ ምክንያቱም ይህን ማድረግ የሚያስችል አቅም አለ! አሁን ላለው ችግር ዳኛው ምርጫ ቦርድ ሳይሆን የፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ ነው፡፡ ለምሳሌ አሁን ያለው ስራ አስፈፃሚ በቁጥር እንኳ የተሟላ አልነበረም፤በዚህ ላይ ከአመራር አሰጣጥ ጋር ተያይይዞ ከባህር ዳሩ ሰልፍ ጋር ተይይዞ የደረሰውን የምናውቀው ነው፡፡ አሁን ያለው አማራጭ እስካሁን ለነበሩ ችግሮች ላይ በጥልቀት በመወያየት መልስ ሰጥቶ ወደፊት ለመራመድ ለዚህም የፓርቲው ከፍተኛው አካል የሆነው ጠቅላላ ጉባኤ ትልቅ መድረክ ነው።