Thursday, 4 June 2015

በምንከተለው የትግል ስልት መተጋገዝ ባንችል እንኳ አንጠላለፍ!

ስርዐቱ በሚወስደው እጅግ የከፋ የአፈና ተግባር ሰላማዊ ትግል በኢትዮጵያ ምድር አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡ ይህ ምንም የሚስተባበል ነገር የለውም የተገለጠ እውነት ነው፡፡ በዚህም የተነሳ በርካቶች ሰላማዊ ትግል ማድረግ አስቸጋሪ ነው በሚል የትግል ስልት እስከመቀየር ተገደዋል፡፡ እያየን እንዳለነው ስርዐቱ ይህንን ጠንክሮ እየሰራበት ይገኛል፡፡ በሰላም ትግል የወንድ በር ሊሰጡት የሚታገሉትን ንፁሃን እንኳ በሽብር ሺፋን ወደ ማጎሪያው ማውረዱን ከቀን ወደ ቀን አጠናክሮ እንደቀጠለ ነው፡፡


 በዚህ የተነሳ ሰላማዊ ትግል ኢትዮጵያ ውስጥ አይሰራም የሚለው ተቀባይነት እንዲያገኝ ስርዐቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ ደፋ ቀና እያለ ይገኛል፡፡ ስርአቱ ከሚከተለው ከፋፍለህ ግዛ እና ብልጣብልጥነት አንፃር ይህን ቢያደርግ ብዙ የሚደንቅ አይደለም፡፡ ይህ ግን ስርአቱን በሚቃወሙት ሃይሎች ሲሆን ጥያቄን ያጭራል፡፡ እስከሚገባኝም ይህ ማስታወቂያ የሚያስፈልገውም ጉዳይ አልነበረም፡፡ ስርአቱ ይህንን አጥብቆ እየሰራበት ያለ ስለሆነ፡፡


 ከፋፋዩ ስርዐት በሰላማዊ ትግል አይወርድም ብለው የሚያምኑ ሃይሎች የመረጡትን የትግል ስልት አከብራለሁ፡፡ ነገር ግን ከነዚህ ወገን በኩል ሰላማዊ ትግል ኢትዮጵያ ውስጥ አያዋጣም ብለው ፕሩፍ ሲያደርጉ እኛም ትጥቅ ትግል እንዲህ እንዲህ ነው ብለን እንዲሁ ሳየሆን መሬት ላይ የሚረግጥ ትንታኔ ማቅረብ አያቅተንም፡፡ ይህ ግን በተጨባጭ ለትግሉ ምን ይጠቅማል ካልን መልሱ ምንም ነው፡፡ ስለዚህም የመረጡትን የትግል ስልት እኛም እንደምናከብረው እነሱም የኛን ያክብሩልን፡፡


 ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ምርጫውን አስመልክቶ ባስተላለፉት መልእክት ህዝብ የወሰደውን የምርጫ ካርድ እንዲቀድ ተናግረው ነበር፡፡ ይህ በተጨባጭ ከምርጫው ፖለቲካ ውጪ ለሆነ ሃይል ምን እንደሚጠቅም አይገባኝም፡፡ ስርዐቱ በምርጫ አይወርድም፡፡ የሚያካሂደው ምርጫ ቧልት ነው ለማለት ከሆነ ምርጫ ካርድ ቅደዱ የሚያስብለበት ምክንያት ግልፅ አይደለም፡፡ ያላደረጁትን ህዝብ፣ ምርጫ ካርድ እንዲወስድ ያልጎተጎቱትን ህዝብ ምርጫ ካርድህን ቀደህ ጣል ማለት ትርጉሙ ምንም ነው፡፡ በዋነኝነት ማለት ቢያስፈልግ እንኳን ይህን ማለት ያለባቸው ነፍጥ ያነገቡ ሃይሎች ሳይሆኑ ሰማያዊዎች ናቸው፡፡


ምንም አንኳን ብረት ያነገቡ ሃይሎች የሚከተሉት የትግል ስልት ሰላማዊ ትግል ከሚከተሉ ሃይሎች መተጋገዝ ባያስችላቸውም መጠላለፍ የለባቸውም፡፡ ብረት በማንሳት ህይወታቸውን ለመስጠት የተዘጋጁ ሃይሎች እንዳሉ ሁሉ አገር ውስጥም ያለውን ከባድ ሁኔታ ተቋቁመው እየታሰሩ፣እየተገረፉ እንዲሁም ውድ ህይወታቸውን ጭምር ለመስጠት እየታገሉ ያሉ መሆናቸውን መርሳት የለብንም፡፡ ሁላችንም ባመንበትና በፈቀድነው መንገድ እንሂድ እናንተም እንዲያው አይ የእኔን መንገድ ለምን አልተከተልክም ማለት ተገቢ አይደለም፡፡


 አሁንም ቢሆን ህዝብን በማደራጀት ለውጥ ማምጣት ይቻላል፡፡ ችግሩ ስርዐቱ ቤት ለቤት ወርዶ የአፈና መዋቅሩን ሲዘረጋ ተቃዋሚዎች ያለምንም ስራ ወደ ምርጫው መግባታቸው፤ ይህንንም ተከትሎ ስርዐቱ ውጤቱን በመጠቅለሉ ሰላማዊ ትግል አብቅቶለታል ሚባለው እያየለ ምምጣቱ ነው፡፡ ይህ የተሳሳተ አተያይ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር በዘንድሮው ምርጫ መሳተፍ የነበረባቸው የተቃዋሚ ፓርቲዎች ከሶስት እስከ አራት የሚበልጡ መሆን አልነበረባቸውም፡፡ አብዛኛዎቹ የመርህ ፖለቲከኞች ናቸው፡፡ የመርህ ፖለቲካ እያራመዱ ቤት ለቤት የደረሰውን የስርዐቱን አፈና ሰብረው ይገባሉ ማለት ዘበት ነው፡፡ ስለዚህ ይህን ሁሉ ሳያገናዝቡ ሰላማዊ ትግል አብቅቶለታል ማለት ስህተት ነው፡፡


 እርግጥ ነው ነባሩ ባህላችን እስኪርቢቶ ከያዘ ሃይል ይልቅ ነፍጥ ያነገበውን እንደሚያጀግንና የተለየ ክብር እንደሚሰጥ ይታወቃል፡፡ እውነታው ግን ሰላማዊ ትግልን የመረጡ ሃይሎች ከሌሎች ያነሰ ወኔ አልያም ቁርጠኝነት ስላነሳቸው እንዳልሆነ ሊሰመርበት ይገባል፡፡ አሁን በተጨባጭ ያለውን እውነት ካየነው ነፍጥ አንግበናል ከሚሉ ሃሎች ይልቅ የአንድነትና የሰማያዊ አባላት እስሩንም ድብደባውን እየተጋፈጡ ይገኛሉ፡፡ በተጨባጭ አሁን ላለው ትግል አይጠቅምም እንጂ በርካታ ምሳሌዎችን እያነሱ ማቅረብ ይቻላል፡፡ ስለሆነም እኛም በመንገዳችን እንሂድ እናንተም በመንገዳችሁ ሂዱ፡፡ በመንገዳችን ባንተጋገዝ እንኳ አንጠላለፍ!
 ጥሩውን ተመኘሁ!

የስፖርት ጋዜጠኞች የተያያዙት ማዝናናት ወይስ ማዘናጋት?

አሁን ባለንበት ጊዜ በኢትዮጵያ ውስጥ ከሁሉም ነገር በሚባል ሁኔታ ጮክ ተብለው የሚወሩት ሁለቱ ነገሮች ናቸው፡፡ አንደኛው የአውሮፓ እግር ኳስ ሲሆን ሁለተኛው ፆታዊ ግንኙነትን የተመለከቱ ርዕሶች ናቸው፡፡ በዚህ ፅሁፍ ለመዳሰስ የፈለኩት በአውሮፓ እግር ኳስ ዙሪያ የመገናኛ ብዙሃንን ያልተገደበ አስተዋዋቂነት ወይም ቲፎዞነት ወይም የማራገብ ሁኔታ መመልከት፤ እንዲሁም የዚህ ማራገብ አስፈላጊነቱ ለምን እንደሆነ መግለፅ ይሆናል፡፡


  ለመነሻ ያህል በአዲስ አበባ ካሉት የራዲዮ ፕሮግራሞች እንኳን ብንጀምር ምን ያህል ሰአት ለአውሮፓ እግር ኳስ እንደሚሰጡ መታዘብ ይቻላል፡፡ ከሌሎች የራዲዮ ፕሮግራሞች አንፃር አብዛኛውን የአየር ሰአት ተሰጥቶት የሚለፈፈው የእስፖርት ፕሮግራም ነው፡፡ በአዲስ አበባ ካሉት ኤፍ ኤም ራዲዮኖች፤ በእንግሊዝኛ ከሚተላለፈው አፍሮ ኤፍ ኤም በተስተቀር አብዛኛው ለእግር ኳስ የሚሰጡት የአየር ሰአት ከፍ ያለ ነው፡፡ እንዲሁ ለእግር ኳስ አልኩ እንጂ ይህም ለሃገር ውስጥ ከሚሰጠው የአየር ሰአት ጋር ሲነፃፀር ሰማይና መሬት መሆኑን ዘወትር የምንታዘበው ነው፡፡ ያንበሳው ድርሻ ለማንችስተርና ለአርሰናል፤ለባርሳና ማድሪድ ወ.ዘ.ተ ይሰጣል፡፡ እዚህ ላይ የአገር ውስጡን ስፖርት እንዲሁ ለቅንነት ያህል ገለፅኩት እንጂ ከማንችስተር እና አርሰናል አንፃር የአየር ሰአት ያገኛል ለማለት እንኳ አያስደፍርም፡፡


 ለምሳሌ ያህል የራዲዮኖቹን አነሳው እንጂ በጋዜጣ የሚታተሙትን እድሜ ጠገቦቹን ኢትዮ ስፖርት፣ ወርልድ ስፖርት፣ዘ-ገነርስ… እማ 95% የሚሆነው የጋዜጣቸው ሽፋን ለአውሮፓ እግር ኳስ እንደሚሰጡ ግልፅ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ማለትም በህትመትና በራዲዮ ካሉት በተጨማሪ ብቸኛው ኢቲቪ(ለነገሩ አሁን ኦሮሚያ ቲቪም የአውሮፓን እግር ኳስን በማስተላለፍ ከኢቲቪ ጋር እኩል እየተጋ ይገኛል፡፡) በነፃ በማስተላለፍ ጠመቃውን እያሳለጡት ይገኛሉ፡፡ አንድ አይነት አካሄድ የሚስተዋልበት ይህ የአውሮፓ እግር ኳስ የጠመቃ አካሄድ ጥርጣሬን ካጫረብኝ ሰንበትበት ብሏል፡፡ እንዳልኩት ሱፐር እስፖርት በክፍያ ኢቲቪና ኦሮሚያ ቲቪ በነፃ በድምፅ እና ምስል የሚያስተላልፉት ሲሆን በራዲዮን በኩል እነ መሰለ መንግስቱ ከሱፐር ስፖርቶቹ ጋዜጠኞች በላይ ሰፊ የአየር ሰአት ወስደው በቀጥታ ያስተላልፋሉ፡፡ ሸገር ኤፍ ኤም ላይም እንዲሁ በየሳምንቱ የሚተላለፍ ፕሮግራም እንዳለ ይታወቃል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የየጨዋታዎቹን ውጤት ተከትሎ ትንታኔ የሚሰጡ ጋዜጠኖች ቁጥራቸው የትየሌሌ ነው፡፡ ለዚህ ይመስላል የአውራምባ ታይምሱ አቤል አለማየሁ በአንድ መፅሃፉ ‹‹አንተ ብቻ የስፖርት ጋዜጠና ሁን›› ሲል የጊዜውን ሁኔታ የገለፀው፡፡


 በየቀኑ የሚሰጡትን የእግር ኳስ የትንታኔ ሰአቶች እንኳን ትተን በሳምንት የሚሰጠውን የቀጥታ ስርጭት ብንመለከት ጉዳዩ ምን ያህል እየተሰራበት እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ለምሳሌ ‹‹እግር ኳስን በራዲዮ ተመልከቱ›› የሚለውን የመሰለን ፕሮግራም ለአብነት ብንወስድ በየሳምንቱ ለአንድ ጨዋታ በትንሹ 90 ደቂቃ የቀጥታ ጨዋታው + ከጨዋታው በፊት 30 ደቂቃ + 30 ከጨዋታው በሁዋላ ያለውን ብንወስድ በድምሩ በሳምንት 2:30 ይወስዳል፡፡ ይህ በወር ሲመታ፣ በአመት ሲመታ ምን ያህል ሊሆን እንደሚችል አስቡት፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከውጤትና ከጨዋታ በፊትና በኋላ ያሉትን ትንታኔዎች የወሰድን እንደሆነ ከአፍሮ ኤፍ ኤም ውጪ በቀን እያንዳንዱ ራዲዮን በትንሹ 2:00 የአየር ሰአት ለአውሮፓ እግር ኳስ ይሰጣል፡፡ ይህን በሳምንት እንዲሁም በወር ሲመታ አስቡት ምን ያህል እንደሆነ!


 የእኔ መከራከሪያ ለምን ስፖርት ተወራ አይደለም፡፡ ጉዳዬ ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት ላይ መነሳትም አይደለም፡፡ እርግጥ ነው መናገር መብታቸው ነው፡፡ ስለ ዋይኒ ሩኒ፣ሜሲ፣ሮናልዶ እድሜ እና ክብደት እንዲሁም ቁመት መናገር ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት ነው ከተባለ መቼስ ምን ይደረጋል፡፡ ጥያቄዬ ስለምን ይህን ያህል የአየር ሰአት ተሰጥቶት ሊወራ ቻለ ነው? ይህንን የሚያግዝ በተጨባጭ ኢትዮጵያ ውስጥ ምን አለ ነው? መቼም አድማጭም ተመልካችም ያለው የአውሮፓ እግር ኳስን ነው፤ የሚል ቀልድ አዘል አስተያየት አይቀርብም አይባልም፡፡ ይህ ቁጥር ነጋ ጠባ እያሻቀበ እንዲሄድና ወጣቱ ስለ ራሱ የወደፊት ሁኔታ ከመጨነቅ ይልቅ ስለ ማንችስተርና አርሰናል እንዲጨነቅ ነጋ ጠባ የሚለፈለፍለት ስለምን ይሆን? መቼም ከዚህ ጀርባ አንድ ድብቅ ሴራ እንዳለ ግልፅ ነው፡፡


ለዚህም ማጠናከሪያ የሚሆነን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የአለም ወንጫ ማጣሪያ ላይ የተከሰተው ድርጊት ነው፡፡ ይህም የኢትዮጵያ ቡድን ሁለት ቢጫ ካርድ ያየ ተጫዋች አላግባብ አሰልፏል ተብሎ 3 ነጥብ እንደተቀነሰበት ሰምተናል፡፡ እዚህ ላይ መነሳት ያለበት የስፖርት ጋዜጠኞች ድርሻ ነው፡፡ የኛ የስፖርት ጋዜጠኞች ምን ይሰራሉ? የነ ሩኒን ፣ የነቫምፐርሲን፣ የነሮናልዶን ወ.ዘ.ተ ከእግር ጫማቸው እስከ እራስ ፀጉራቸው ሲለፈልፉልን ስለምን ስለአገራቸው እግር ኳስ ቢያንስ በ90 ደቂቃ ውስጥ የተመዘዘውን ቢጫ ካርድ መዝግበው መያዝ አቃታቸው? የአርሰናሉ ኮሶሎኒ በሁለት ቢጫ ካርድ ምክንያት በሚቀጥለው ጨዋታ አይሰለፍም፣ ሜሲ እዚህ አገር ተወልዶ እንትን በምትባል መንደር አድጎ ቁመቱ ይህን ያህል ክብደቱ ይህን ያህል የሚሉን የስፖርት ጋዜጠኞች ስለምን የኛን ቡድን የ 90 ደቂቃ ቢጫ እንኳ መቁጠር አቃጣቸው ብለን ስንጠይቅ ሴራው ፍንትው ብሎ ይታየናል፡፡ በማስታወቂያ በኩል ያለውን ብንመከት ድርጅቶች ስፖንሰር የሚያደርጉት የእስፖርት ፕሮግራሞችን 90% ያለፈ መሆኑን ሌሎች ፕሮግራሞች ባንፃሩ የማስታወቂያ ድርቅ ሲመታቸው እንመለለከታለን፡፡ ምነው ይህን ያህል እዚህ አገር ሳናውቀው ኳስ ተዘርቶ ኳስ መታጨድ ተጀመረ እንዴ?


 ምንአልባት በደምብ አልገለፅኩት ይሆናል አንጂ አሁን ያለው ሁኔታ እጅግ አስከፊ ወደ ሆነ አዘቅት ውስጥ የሚከተን ይሆናል፡፡ አንድ ታዳጊ አገር ያውም ከድህነትና ከችጋር ያልተላቀቀች አገር ውስጥ የተማሩና ገና የመጀመሪያ ደረጃ ትምርታቸውን ያልጨረሱ አፍላ ወጣቶች ሳይቀሩ በአውሮፓ እግር ኳስ ተጠምደው ነጋ ጠባ የሚያሳስባቸው የክለቦቹ መሸነፍና ማሸነፍ ሲሆን ወዴት እየሄድን እንደሆነ እና ሴራው ግቡን እየመታ መሆኑን እንረዳለን፡፡ በየመስሪያ ቤቱ ስለ አውሮፓ እግር ኳስ ሲከራከሩ ከፍ ሲልም ሲደባደቡ መመልከት ብዙም የሚያስደንቅ አይደለም፡፡ ተማሪዎችም በእረፍት ግዜያቸው ሰብሰብ ብለው ሲያወሩ የሚሰሙት ስለ እግር ኳስ ከሆነ አመታት ተቆጠሩ፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪዎች ሳይቀሩ የመጀመሪያው ወሬያቸው ስለተሰጣቸው የቤት ስራ ሳይሆን ስለ ማታው ጨዋታ ከሆነ ቆየ፡፡ ገና 10 እና 11 አመት ያልሆናቸው ልጆች ስለምን ስለ አርሰናል እና ማንችስተር ነጥብ መጣል እንዲሁም ስለ ተጫዋቾች ጉዳት እንዲጨነቁ ተፈረደባቸው?



ገና ከወዲሁ ትውልዱን በአንድ አይነት አካሄድ የመቅረፅ ሴራ… ከፍ ያለውንም እንዲዝናና ሳይሆን መሬት ላይ ያለውን እውነት እንዳያይ ማዘናጋት የስፖርት ጋዜጠኖች ድርሻ ከሆነ ቆየ፡፡ ጋዜጠኞቹም ገንዘብ እስካገኙ ድረስ የትውልዱ እጣ ፋንታ ግድ የሚሰጣቸው እንዳልሆነ አሳይተውናል እያሳዩንም ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ከቀጠለ እነሆ ማን ነው ይችን አገር የሚረከባት? መቼም 4-4-2 አሰላለፍ በስነ-ምግባርና በእውቀት የታነፀ ትውልድ ለመቅረፅ ቀርቶ ቤተሰብን ለመምራት እንኳ አያገለግልምና የትውልዱ ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ነው፡፡ ምን ብናረግ ትውልዱን ከዚህ አይነት አፍዝዝ አደንዝዝ ሴራ ማውጣት እንችላለን? የሚለው የሁሉም የአገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ድርሻ በመሆኑ፤ ለዚህ ሴራ መክሸፍ የበኩላችንን በማድረግ ትውልዱን ልናድነው ይገባል፡፡
 ግሬስ አባተ